Main Article Content

የትብብር ብልሃታዊ ማንበብ ዘዴ (Collaborative Strategic Reading) የአማርኛ ቋንቋ አፍፈት ተማሪዎችን አንብቦ የመረዳት ችሎታ፣ የማንበብ ተነሳሶትና የትብብር ክሂል የማሳደግ ፋይዳ


ማስተዋል ውበቱ

Abstract

የዚህ ጥናት አላማ የትብብር ብልሃታዊ ማንበብ ዘዴ የአማርኛ ቋንቋ አፍፈት ተማሪዎችን አንብቦ የመረዳት ችሎታ፣ የማንበብ ተነሳሶትና የትብብር ክሂል ለማሳደግ ያለውን አስተዋጽኦ መፈተሽ ነው። ቅድመትምህርት ፈተናና ድህረትምህርት ፈተና የቁጥጥር ቡድን ፍትነትመሰል የምርምር ስልት ተግባራዊ ሆኗል። የጥናቱ ተሳታፊዎች በባህር ዳር ከተማ በካቲት 23 የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርትቤት የ2010 ዓ.ም የሰባተኛ ክፍል ተማሪዎች ናቸው። የፍትነቱ ቡድን ተሳታፊዎች (44 ተማሪዎች) በትብብር ብልሃታዊ ማንበብ ዘዴ፣ የቁጥጥሩ ቡድን ተሳታፊዎች (46 ተማሪዎች) ደግሞ በክፍል ደረጃው የመምህር መምሪያና የተማሪ መጽሀፍ በተመለከተው መሰረት ተለያይተው ለአስር ክፍለጊዜያት አንብቦ መረዳትን ተምረዋል። የቅድመትምህርትና የድህረትምህርት አንብቦ የመረዳት ችሎታ፣ የማንበብ ተነሳሶትና የትብብር ክሂል መጠናዊ መረጃዎች በፈተናና በጽሁፍ መጠይቆች ከሁለቱም ቡድኖች ተሳታፊዎች፣ እንዲሁም የድህረትምህርት አይነታዊ መረጃዎች በቡድንተኮር ውይይት ከፍትነቱ ቡድን በቀላል እጣ ከተመረጡ አምስት ተማሪዎች ተሰብስበዋል። መጠናዊ መረጃዎች በባለብዙ ተላውጦ ልይይት (one way multivariate analysis of variance))፣ የቡድንተኮር ውይይት መረጃዎች ደግሞ በጭብጥ ትንተና (thematic analysis) ተተንትነዋል። ውጤቱ እንዳመለከተውም በድህረትምህርት አንብቦ የመረዳት ችሎታ (F(1, 88) = 10.436, p = .002) እና በትብብር ክሂል (F(1, 88) = 18.653, p = .001) አንጻር የፍትነቱ ቡድን ተሳታፊዎች ከቁጥጥሩ ቡድን ተሳታፊዎች በልጠው ጉልህ መሻሻል አሳይተዋል፤ የቡድንተኮር ውይይት መረጃዎቹም  እነዚህን ውጤቶች አጠናክረዋል። በድህረትምህርት የማንበብ ተነሳሶት ውጤት የፍትነቱ ቡድን ተሳታፊዎች በመጠኑ ከፍ ብለው ቢገኙም፣ በቤንፌሮኒ የጉልህነት ማስተካከያ መሰረት ሲሰላ ውጤቱ (F(1, 88) = 3.450, p = .067) ጉልህ ልዩነት አለመኖሩን አሳይቷል። ከዚህም፣ የትብብር ብልሃታዊ ማንበብ ዘዴ አንብቦ የመረዳት ችሎታንና የትብብር ክሂልን ለማሳደግ አዎንታዊ ተጽእኖ እንዳለው ታውቋል። የማንበብ ተነሳሶትን በማጎልበት አንጻር ግን ዘዴው ጉልህ ተጽእኖ እንደሌለው ለመረዳት ተችሏል።


 


Journal Identifiers


eISSN: 2518-2919