Main Article Content

የአማራጭ ምዘናዎች የተማሪዎችን ድርሰት የመጻፍ ችሎታ የማሻሻል ሚና


ኃይላይ ተስፋይ
ማረው ዓለሙ
ሙሉጌታ ተካ

Abstract

የዚህ ጥናት ዓላማ የአማራጭ ምዘናዎች የተማሪዎችን ድርሰት የመጻፍ ችሎታ የማሻሻል ሚና መመርመር ነበር፡፡ ዓላማውን ከግብ ለማድረስም፣ በ2009 ዓ.ም ከአርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ ቋንቋ(ዎች) እና ስነጽሑፍ-ዐማርኛ ትምህርት ክፍል አንደኛ ዓመት ተማሪዎች በቅድመትምህርትና በድኅረትምህርት ድርሰት የመጻፍ ችሎታ ፈተናዎችና በድርሰት የመጻፍ ችሎታ ሂደታዊ ዕድገት መመዘኛ መሥፈርቶች አማካይነት መረጃዎች ተሰብስበዋል፡፡ መረጃዎቹ ለትንተና ከመቅረባቸው በፊት ተጣርተው፣ ለትንተና በሚያመች መለያ ስያሜ ተሰጥቷቸዋል፡፡ ከዚያም ከድርሰት የመጻፍ ችሎታ የቅድመትምህርትና የድኅረትምህርት ፈተናዎች የተገኙት አማካይ ውጤቶችና መደበኛ ልይይቶች በገላጭ ስታትስቲክስ ከተፈተሹ በኋላ፣ አጠቃላይ ድርሰት የመጻፍ ችሎታ ውጤቶች በጥንድ ናሙና ቲ-ቴስት፣ ንዑሳን የመጻፍ ችሎታዎች ውጤቶች ደግሞ በዊልኮክሰን ስሌት ተተንትነዋል፡፡ በድርሰት የመጻፍ ችሎታ ሂደታዊ ዕድገትም በጊዜ ክትትሎሽ (Time series)፣ እንዲሁም መጠናዊ ልዩነቱን ለማየት፣ በዳግም ልኬት ልይይት ተፈትሿል፡፡ በዚህም መሠረት የተማሪዎች አጠቃላይና ንዑሳን ድርሰት የመጻፍ ችሎታዎች የድኅረትምህርት አማካይ ውጤቶች ከቅድመትምህርት አማካይ ውጤቶች ተሽለው ተገኝተዋል፡፡ በሂደታዊ የመማር ዕድገትም በየደረጃው የተገኙ አማካይ ውጤቶች ዕድገት እንዳለ አሳይተዋል፡፡ ይህም የአማራጭ ምዘናዎች የተማሪዎችን ድርሰት የመጻፍ ችሎታ በማሻሻል ረገድ አዎንታዊ ሚና እንዳላቸው አሳይቷል፡፡ የጥናቱ አንድምታም ተግባርተኮር ድርሰት የመጻፍ ትምህርት በአማራጭ ምዘናዎች መታገዝ እንዳለበት አመላክቷል፡፡ በዚህም መሠረት አዋጭነት ያላቸው የድርሰት ማስተማሪያ ዘዴዎችና የትግበራ ሂደቶች ተጠቁመዋል፡፡


Journal Identifiers


eISSN: 2518-2919