Main Article Content

አማርኛን በሁለተኛ ቋንቋነት የመማር ተነሳሽነትና የውጤት ተዛምዶ፤ በጋሞኛ ቋንቋ አፍፈት ተማሪዎች


ዘሪቱ አስፋው
ማረው ዓለሙ

Abstract

ጥናቱ በዋናነት በጋሞኛ ቋንቋ አፍፈት ተማሪዎችን አማርኛን በሁለተኛ ቋንቋነት የመማር ተነሳሽነትና የውጤት ተዛምዶ መርምሯል፡፡ ተሳታፊዎች በጋሞ ጎፋ ዞን በአርባ ምንጭ ሁለተኛ ደረጃና መሰናዶ ትምህርትቤት በ2003 ዓ.ም 207 የ9ኛና የ10ኛ ክፍል ተማሪዎች ናቸው፡፡ ከእነሱም በጽሑፍ መጠይቅና በፈተና መረጃዎች ተሰብስበዋል፡፡ በመረጃዎቹ ትንተና መሠረትም በጋሞኛ ቋንቋ አፋቸውን የፈቱ ተማሪዎች በቡድን አማርኛን በሁለተኛ ቋንቋነት የመማር ተነሳሽነት አሳይተዋል፡፡ በተቃራኒው ግን በተማሪዎቹ አማርኛ ቋንቋ የመማር ተነሳሽነትና በቋንቋው ትምህርት ውጤት መካከል ተዛምዶ አልታየም፡፡ በተመሳሳይም በተነሳሽነት ዓይነቶችና በአማርኛ ቋንቋ ትምህርት ውጤት መካከል ተዛምዶ አልታየም፡፡ ይሁን እንጂ በውስጣዊና በውህዳዊ፣ በውስጣዊና በውጫዊ፣ በውስጣዊና በጥቅማዊ ተነሳሽነቶች መካከል በስታቲስቲክስ ጉልህ ተዛምዶ (P<0.05) ታይቷል፡፡ በተጨማሪም ውስጣዊ፣ ውህዳዊ፣ ውጫዊና ጥቅማዊ ተነሳሽነቶች፣ ፆታና የከፍል ደረጃ በጥምር በአማርኛ ትምህርት ውጤት ላይ ጉልህ ድርሻ (አስተዋፅዖ) እንዳላቸው የጥናቱ ውጤት አሳይቷል፡፡ በሌላም በኩል የክፍል ደረጃ የትምህርት ውጤትን ወሳኝ ሆኖ ሲገኝ በዚህ ረገድ የውስጣዊና የውጫዊ ተነሳሽነቶች አስተዋፅዖ የጎላ አልሆነም፡፡ ከዚህም ሌላ በሁለተኛ ቋንቋ የመማር ተነሳሽነትና በፆታ መካከል ተዛምዶ እንዳለና ጥቅማዊ ተነሳሽነት፣ ፆታና የክፍል ደረጃ የአማርኛ ትምህርት ውጤት ተንባይ ሆነው መገኘታቸውን የጥናቱ ውጤት አመላክቷል፡፡ በጥናቱ ውጤት መሠረትም የመፍትሄ ሀሳቦች ተጠቁመዋል፡፡


Journal Identifiers


eISSN: 2518-2919